TRACK
‘’ያሉ ግጭቶችን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት በመንግስትም ሆነ በታጣቂዎች በኩል እውነተኛ ፍላጎት የለም’’ የፖለቲከ ፓርቲዎች የጋራ ም/ቤት
ነሐሴ 9፣2016
የኢትዮጵያ የፖለቲከ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት፤ ‘’በኦሮሚያ እና በአማራ ክልሎች ያሉ ግጭቶችን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት በመንግስትም ሆነ በታጣቂዎች በኩል እውነተኛ ፍላጎት የለም’’ አለ፡፡
‘’በሁለቱ ክልሎች ባለው ግጭት ምክንያት ንጹሃን እየሞቱ፣ እየተፈናቀሉ፣ እየታገቱ እና ንብረታቸው እየወደመ መሆኑን መንግስትም ሆነ በጫካ ያሉ አካላት እያወቁ ችግሮቻቸውን በንግግር ለመፍታት ግን ፍላጎት የላቸውም’’ ሲሉ የጋራ ምክር ቤቱ ሰብሳቢ ደስታ ዲንቃ ተናግረዋል፡፡
‘’ይህም መንግስት እየመራሁት ነው፣ ጫካ ያሉ አካላት ደግሞ እየታገልኩለት ነው ለሚሉት ህዝብ ያላቸውን ምልከታ ያሳያል’’ ተብሏል፡፡
መንግስት በተደጋጋሚ በኦሮሚያም ሆነ በአማራ ክልል፤ ነፍጥ አንስተው ጫካ ገብተው ከሚታገሉ አካላት ጋር ችግሮችን በንግግር ለመፍታት ዝግጁ መሆኑን በተደጋጋሚ ተናግሯል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች አሁን ኢትዮጵያ ካለችበት የግጭት አዙሪት መውጫው መንገድ ንግግር እንደሆነ ደጋግመው ሲናገሩ ተሰምቷል፡፡
የኢትዮጵያ የፖለቲከ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ግን ‘’በኦሮሚያ እና በአማራ ክልሎች ያሉ ግጭቶችን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት በመንግስትም ሆነ በታጣቂዎች በኩል፤ እውነተኛእ ከልብ የመነጨ ፍላጎት የለም’’ ሲል ተናግሯል፡፡
Comments