ጥቅምት 27 2018
በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች በተከሰቱ ግጭቶች ምክንያት መስተጓጎል ከሚገጥማቸው አንዱ የህክምና አገልግሎትን በአግባቡ አለማዳረስ ነው፡፡
በእነዚህ አካባቢዎች እንዲሁም በግጭት ባለፉት ውስጥ ደግሞ የአዕምሮ ጤና ችግር እየተባባሰ የሚሄድ በመሆኑ ህክምናው እንዲሁም የመድኃኒት አቅርቦቱ ላይ እንዴት እየተሰራ ነው? ስንል የጤና ሚኒስቴርን ጠይቀናል፡፡
በጤና ሚኒስቴር የአዕምሮ ጤና ፕሮግራም ባለሙያ የሆኑት አቶ ጀማል ተሾመ እንደነገሩን በተለያዩ ግጭት በነበረባቸው እንዲሁም አሁንም ድረስ ግጭቱ በቀጠለባቸው አካባቢዎች ላይ ከመንግስት በተጨማሪ በአለም አቀፍ ተቋማት ጭምር የአዕምሮ ጤና ህክምናና የመድኃኒት አቅርቦት እንዲኖር ጥረት እያደረግን ነው ብለዋል፡፡
የአዕምሮ ጤና ህክምና አንዴ ከተቋረጠ እየተባባሰ የሚሄድና ለነገ ቢባል የህብረተሰብ ጤና ችግር ሆኖ የሚዘልቅ በመሆኑ በወረዳዎች ከሚገኙ ጤና ጣቢያዎች ጀምሮ አገልግሎቱ እንዲሰጥ እየተደረገ ነው የሚሉት አቶ ጀማል ግጭት እንዲሁም ተፈናቃዮች ባሉባቸው አካባቢዎችም ላይ እንዳይቋረጥ የተለያዩ ስራዎች እየተከወኑ መሆኑን ይናገራሉ፡፡
በተለይ ከመድኃኒቶች አቅርቦቱ ጋር በተያያዘ እጥረት እንደሚታይ ብዙ ጊዜ የሚነሳ ችግር መሆኑን የሚናገሩት ባለሙያው በድንገተኛ አደጋዎች ምክንያት ከሚያጋጥሙ የቅርቦት መስተጓጎሎች በተጨማሪ ግን ህክምናውን የሚሰጡ ተቋማት በሚፈልጉት መጠን ፍላጎታቸውን አለማሳወቃቸው ሌላው ችግር መሆኑን ይጠቅሳሉ፡፡
Comments