ጥቅምት 18 2018
መንግስት “ጽንፈኛ እና አሻባሪ” የሚላቸውን ቡድኖች ከመውጋት ባለፈ ፖለቲካዊ መፍትሄ ለመስጠት ለምን እንደማይሰራ ተጠየቀ፡፡
ጥያቄው የቀረበው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ከምክር ቤት አባላት ለሚነሱ ጥያቄዎች ምላሽ እና ማብራሪያ ለመስጠት በህዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤት በተገኙበት ወቅት ነው፡፡
የአብን ፓርቲ ተወካዩ የምክር ቤት አባል ደሳለኝ ጫኔ (ዶ/ር) በአማራ፣ በኦሮሚያ እና በሌሎች ክልሎች ያሉ ግጭቶች እና ጦርነቶች ተባብሰው በመቀጠላቸው ብዙዎችን እየጎዱ ነው ብለዋል፡፡
መንግስት የጸጥታ ችግሮችን ለመፍታት ጽንፈኛ እና አሻባሪ የሚላቸው ቡድኖች ከሙውጋት ባለፈ ለሁለቱ ክልሎች ማለትም ለአማራ እና ኦሮሚያ ክልሎች ከወታደራዊ አማራጭ ውጪ የተለየ ፖለቲካዊ መፍትሄ ለመስጠት ለምን እንደማይሰራ ጠይቀዋል፡፡
የኢትዮጵያ ህዝብ የእርስ በእርስ ጦርነት አንገፍግፎታል፣ በአገር ውስጥ ተንቀሳቅሶ መስራት እና ሰርቶ መብላትም ከብዶታል ፣ አገራችንም እንደ ኮሎምቢያ 50 ዓመታትን እየተዋጋች ልትቀጥል አትችልም ሲሉ ደሳለኝ ጫኔ (ዶ/ር) ተናግረዋል፡፡
Comments